-
“Let's build bridges, not walls.” Martin Luther King, Jr. — Visit my blog: https://dildiy.net/ — ድልድይ - ግላዊ እይታና ጥልቅ የመሻገሪያ እሳቤዎች የሚጋሩበት ከንባብ፣ ከኑረት እና ከምናብ የሚቀዱ ንሸጣዎች መድረክ ነው። - ሃሳቦቹ ከየትኛውም የአስተሳሰብ ጎራ (ism) አይወግኑም!! — Concern & Concept — D.S.
[የቀጠለ...]
.
.
.
⬜️ ስነ-ልቦናዊ ጥላ (The Shadow Self)
ካርል ዩንግ እንደሚለው፣ በሰው ላይ በብርቱ አኳኋን የምንተቸው ነገር እኛ ውስጥ ተደብቆ ያለ "ጥላ" ነው... በሌላ አነጋገር ሌላውን "ኩሩ" የምንለው፣ እኛ ውስጥ ያለውን ድብቅ ኩራት ስለለየን ነው... ሌላውን የምንጠረጥረው እኛ ውስጥ አጋጣሚውን ቢያገኝ ከጥፋት የማይመለስ ስብዕና እንዳለ ስለተገነዘብን ነው... [ችግር አለብን ብለን ግን አንቀበልም]
"Projection is one of the commonest psychic phenomena... Everything that is unconscious in ourselves we discover in our neighbor, and we treat him accordingly." — Carl Jung
"Yesterday I was clever, so I wanted to change the world. Today I am wise, so I am changing myself." — Rumi
.
.
.
1️⃣
በውጭ ሃገር የሚኖር 'የማላውቀው' ሰው "ገጽህ ላይ የምትጽፋቸው ጽሑፎች ያስደስቱኛል" በሚል ምክንያት ብቻ የቴሌግራም Premium package ገዛልኝ...
2️⃣
ባለፈው ባነበባችሁት የአንዲት ሼፍ የምስጋና ጭረት ልቧ የተነካ ወዳጄ - ከወደ ዱባይ ልብ የሚያሞቅ Tip ለባለታሪኳ በመላክ ደግነት አሳየችኝ...
3️⃣
ትናንት ማምሻ ደግሞ ካፌ ውስጥ አንዲት ልጅ የአገልግሎት ሂሳቤን ዘግታ መውጣቷን አስተናጋጇ ነገረችኝ - 'በድልድይ ስም ተከፍሏል' ማለቷን አክላ...
['እንዴት አወቀችኝ?' የሚል ጥያቄ ሲፈጠርብኝ በራሴ አፍሬ እንደነበር አልሸሽጋችሁም]
____
🤎 የሰው ልጅ ልብ በስጦታው ልክ ይታያል ብዬ ልሞግታችሁ አልደፍርም - ስጦታውን በወለደው ሰበብ (Intention) ውስጥ ንጹህ ፍቅር እንዳለ ግን መካድ አይቻልም... በዚህች ዓለም ደግሞ ምንም ነገር በቅቶን አያቅም - ከፍቅር ውጪ...
እናም...
❗️
የሚገጥሙኝ ብዙ ሰዎች ደጋግና ቀና ሆነው ሳለ በአንዳንድ ሰዎች ስህተት ላይ Dwell የማድረግ ዝማሜዬ መልሶ እኔኑ ያናድደኛል...
____
⚡️ ወዳጆቼ - ሕይወት ውብ ናት - ውብ ሰዎችም አሉባት!!
____
“Be the reason someone smiles. Be the reason someone feels loved and believes in the goodness of people.” — Roy T. Bennett
የመጀመሪያው ጠዋት...
የካንቲኗ ንጽሕና እንከንየለሽ ነው... ሞገስ አለው... የዕቃው አቀማመጥ፣ የጠረጴዛና ወንበሩ አደራደር፣ የክፍሉ ጠቅላላ ድባብ፣ መዓዛው የመብላት አምሮትን ይቀሰቅሳል... የእናት ቤት ያስረሳል... [እዚህ ሌላ እናት አለች...]
በኮይሻ ካንቲን ውስጥ መመገብ የራበውን ሆድ ከምግብ ጋር ከማገናኘትም በላይ ረቂቅ ነው... መንፈስህ ይረካል... ዓይንህ ውበት ይሞላል... ምላስህ የጣዕም ጥጉን ይደርሳል...
በማይቋረጥ ትህትና፣ በማይበላለጥ አክብሮት፣ በማይሰክን ብርታት፣ ሰርክ አዲስ በሆነ ትጋት መስተንግዶ ይጠብቅሃል...
ሌላ ቀን ከሰዓት...
ሰው እንዴት ሁሌና ለሁሉም ሰው መልካም ይሆናል?... ሰው እንዴት በማይናጠብ ትህትና ከሄደ ከመጣው ጋር ይዋባል?... ምን ዓይነት ልብ ነው ይሄ?... ምን ዓይነት ርቀት ነው የምር?...
ሁሉን ወዶ፣ በሁሉ ተወዶ መገኘት ልምድ ይወልደዋልን?... በየሰው ልብ ውስጥ ያለ ልዩነት ቦታ ማግኘት ሰውነት ይቀርጸዋልን?... አይመስለኝም - ይሄ አንዳች ዓይነት መንፈሳዊ ተውህቦ ያለው ተፈጥሮአዊ ልገሳ ነው...
ኮካ ይህ ብርቅ ጸጋ በተግባሯ ላይ ብቻ ሳይሆን በሁለንተናዋ ላይ ፈስሶላታል... እያየችህ ባልሆነ ጊዜ እንኳ የእናትነት መንፈሷ ይረብብሃል... ካንቲኑ በሰው ተሞልቶ ባለበት ሁኔታ እንኳ ሁሉም ሰው እንደ ሃጃው የሚገነዘበው ስሜት ከየእንቅቡ ይደርሳል...
ብዙዎቻችን በዚህ የስሜት ከፍታ የምናውቀው እናታችንን ብቻ ነው... ኮካን ያዩ ሰዎች ደግሞ ለሁሉም እናት መሆን የተቻላት ስለመሆኗ በግልጽ ይመሰክራሉ...
የሆነ ቀን ምሽት...
ያ ቀኑን ሙሉ በነዲድ ፀሐይ ሲጣፋ፣ ከብረት ጋራ ሲላፋ፣ ከኮንክሪት ጋር ሲጋፋ፣ በዳገት ቁልቁለቱ ሲገፋ የሚውልን ባለሙያ አስቡት...
የዛለ ጡንቻውን፣ የደከመ ገላውን፣ የተበተነ ሃሳቡን በአዕምሮአችሁ ሳሉት... ምን አበርትቶት ነው ታዲያ ወደ ስራ የሚመለሰው?... ምን ፈውስ ሰጥቶት ነው መሳሪያውን ዳግም የሚያነሳው?...
የብርታቱ አንዱ ምንጭ የኮካ ማዕድ ነው... ሰዓት ደርሶ ወንበር ሲስብ፣ ትንፋሽ ወስዶ ኮካን ሲያስብ - ልቡ የማይረሰርስ፣ በሚቀርብለት ማዕድ የማይፈወስ የለም...
እርሷ ንድፍ ከሚያወጡ መሃንዲሶች፣ ከሚገነቡ እጆች እኩል ለቦታው ቁልፍ ነች... በዚያች የ NASA ጽዳት ሰራተኛ ንግግር ውስጥ ካየናት ደግሞ 'የኃይል ማመንጫ ግድብ እየገነባች ነው'... ግድቡ ሜጋዋቶችን ያመነጫል - እርሷ ሰብዓዊነትን ትረጫለች...
ከመጀመሪያው ቀኔ ጀምሮ እንዳስተውላት የሚያደርግ ሞገሷን ለመገንዘብ አልሰነፍኩም... ለነገሩ እንዴትስ ይቻለኛል?... የኮካ ጸባይ እኮ የማይደብቁት ፀሐይ ነው... ለሁሉ ይታያል...
በፊት ገጿ ላይ በሚበራ የፈገግታ ፀዳል እንዳዩዋት ያውቋታል... በእጇ ሙያ በምግቧ ጣዕም፣ በሙያ ያደንቋታል... ብሉ ጠጡ ስትል በድምጽ፣ እንደ እናት ይለይዋታል...
____
የመጨረሻው ቀን...
ተግባራችን ተፈጽሞ መለየታችን ግድ ሆነ... ቁርሳችንን በልተን ስንወጣ ልንሄድ መሆኑን ሰማች... ከኩሽናዋ ስትሮጥ ወጥታ በቆዘመ ልብ አናገረችን...
'ልትሄዱ ነው እንዴ?'
'አዎን' መከፋቷ ተጋብቶብን
'ስንቅ ሳልቋጥርላችሁ?' ከፋት
___
አንድ ቀን፣ ይመስለኛል ቁርስ እየበላን ነው፤ እንክብካቤዋ ከልክ በላይ ሲሆንብኝ፣
'እናት እኮ ነሽ' አልኳት
'ነኝ እኮ ታዲያ - ልጆች አሉኝ' አለችኝ... ለእኛ እናት መሆኗን መቀበል ከብዷት
'ልክ ነሽ፣ እዚህም ግን ልጆች ወልደሻል' አልኳት - የመልካም መንፈሷ ተቋዳሽ መሆናችንን ላስታውሳት...
___
ለመንገድ ብላ የቀረቀበችልንን ሁሉ መኪናችን ላይ ጫንን... ተሰናብተናት ጉዞ ጀመርን...
ብዙ፣ ብዙ፣ ብዙ ራቅን...
ዓይኖቿ ዓይኔ ላይ ተመላለሱብኝ፣ እናትነቷ፣ ሩህሩህነቷ፣ የፊቷ ገጽታ፣ ዓይኔ የሚያየውም - ልቤ የሚረዳውም ሁሉነቷ፣ እንደ ጽላሎት እንደተከተለኝ ገባኝ...
ሰው ጠግቦ የበላ የማይመስላት - እናት!...
ሁሉን የምትስብ - መፍቀሬ ሰብ...
ሁሉ የሚወዳት - ሒሩት!...
____
አንዳንዴ እጃችን ላይ ኖሮ በቅጡ ያልተገነዘብነውን ጣዕም፣ ውጣ ውረዳችንን ሳይሻ በቀላሉ የተከሰተልንን ጥቅም for granted እንወስዳለን... እንደነገሩ እንተዋለን... 'ምን አዲስ ነገር አለው?' ብለን እናሳንሳለን... እንዲህ እያልን በጎ ልቦችን እንሰብራለን... ውብ ጅምሮችን እንገድላለን...
____
አንድ ነገር ልለምናችሁ...
ቅን ልቡ ለሚነካችሁ - ለእርሱ፣ ቅን ልቧ ለሚያርሳችሁ - ለእርሷ ይህንን የደግ ሰው ሃቲት ላኩለት/ላት... አንዲት ነፍስ ተውባ ልባችንን ደስ ስታሰኘን ካላመሰገንን ሌሎች ደጎች አይፈጠሩም፣ ውቦቹም በውብነታቸው አይጸኑም... አጋጣሚ ፈልገን 'አበጀህ ጎሽ' ካላልን፣ ምክንያት ሽተን ካላደነቅን የየልቦቻችን በረሃማነት የሰደድ ምንጭ ሆኖ ያጠፋናል...
____
ይህ ማስታወሻ - በየነፍሳችን ደጀ ሰላም ድንገት ተከስተው የደስታችንን ማድጋ ለሞሉ፣ በመኖር አንድ ቀን ለአፍታ ሳቃችን ሰበብ ለሆኑ ሰዎች መዘከሪያ እንዲሆን ተጫረ...
____
@bridgethoughts
🗣️
.
.
.
ያላዩህ ያዩህ'ለት
.
.
.
“If a man is called to be a street sweeper, he should sweep streets as Michelangelo painted, or Beethoven composed music, or Shakespeare wrote poetry.
He should sweep streets so well that all the hosts of heaven and earth will pause and say, 'here lived a great street sweeper who did his job well'.” ~ Martin Luther King Jr.
____
"አንድ ሰው መንገድ ጠራጊ ነው ከተባለ... ሚካኤልአንጀሎ ረቂቅ ስዕሉን ሸራ ላይ በሚያትምበት ውበት፣ ቤትሆቨን ሙዚቃውን በሚያስማማበት ጥልቀት፣ ሼክስፒር ቅኔውን በሚያራቅቅበት ልኬት መንገዱን መጥረግ አለበት... ይህን ካደረገ የሰማይ አጋፋሪዎችም ሆኑ የምድር ተመላላሾች በዚያ ቆመው 'እዚህ ጋ ኃላፊነቱን በቅጡ የሚወጣ ጎበዝ መንገድ ጠራጊ አለ' ይላሉ"
____
❓ የአበርክቶህን ውበት የምትስልበት የአንተ ሸራ ምንድነው?... ተመልካቹን የሚያስደስት ያንተስ ውበት ወዴት ነው?... ልብህ ትረካበት ዘንድ የአንተ ግብር ምንድነው?...
____
✍️ ድብቁን ውበት ይገልጽ ዘንድ ግልጹን መጥረጊያ ለማንሳት አታመንታ... በሌለህበት ስላንተ ይመሰክር ዘንድ አጠራረግህን ከልብ አድርግ...
____
@bridgethoughts
⭐️
የሚያየኝ እንደሌለ ባወቅሁ ጊዜ ዓይኖቼን በዕንባ ሞላሁ... የሚሰማኝ እንደሌለ ሲገባኝ በእሪታ ዙሪያዬን አናጋሁ... የሚጠይቀኝ እንደሌለ ስገነዘብ ከአውላላ ተንጋለልኩ...
እፎይ...
አንዳች ዕዳ ከውስጤ ሲመነጨቅ ተሰማኝ...
ቆይታዬ በረዘመ ቁጥር ተመስጦዬ እየጠጠረ ሄደ... ያለሁበትን ስዘነጋ የጨረቃ ወግ ከበደ...
ይገርማል...
ዘግይተው ካለሁበት የደረሱ ሁሉ እብድ ነው ብለው ይሸሹኝ ነበር...
በምሽቱ ፍካት፣ በጨረቃ ውበትና በከዋክብት ንፃት የተመሰጡ ዓይኖቼን ሊያስተውል የፈቀደ አልነበረም - ከእርሷ በቀር...
ፍቃዴን ሳትጠይቅ፣ ለልብሷ ሳትጠነቀቅ፣ ስለ ትውውቃችን ሳትጨነቅ መጥታ ጎኔ ተንጋለለች...
እኔኑ መሰለች!!...
የሙዚቃው ምት አልተረበሸም... የምሽቱ ወግ አልተናጠበም... ይልቁን ታደመችበት... ሳትደናገር አዜመችው... ከደረሰችበት ቀጠለችው... አብራኝ ዘመረች...
[ዜማውን እንዴት አወቀች?... ስንኙን እንዴት አለችው?... እስከዚያች ቀን ድረስ የኔ ብቻ አልነበረምን?...]
ጨረቃ ደስ አላት... ከዋክብትም አረገዱ...
ሆኖም...
የእንግዳዬ ብርሃን ያፈካው ዙሪያዬን ሲመለከቱ በዚያ መቆየት እንደሌለባቸው ገብቷቸው ነበር...
ይሄኔ... ልቤ ወደ ጆሮዬ አስግጋ እንዲህ አንሾካሸከች...
"ልቧን ወድጄዋለሁ፤ ምታችን ሲጣጣም ተሰምቶኛል..."
ልቤን አመንኳት... ዓይኖቼ ወደ ውስጤ ማየት መጀመራቸውን አስተውዬ ነበርና...
____
@bridgethoughts
.
.
.
እናም...
እንዲሁ እየተፎጋገርን ሌላ መስከረም ይጠባል... እንዲሁ እያስመሰልን ሌላ ክረምት ይመጣል... ማልገጥ ትትርና እንደሆነልን መሰንበቻው ይቆጥራል...
ልቦቻችን እየተዋወቁ በአንደበት ልክ እንካካዳለን... ተግባራችን ጮሆ እየተናገረ በቃል ድርድር ትጉህ እንመስላለን...
ከእያንዳንዱ እንቅስቃሴ ትርፍ እንዲቆየን፣ በእያንዳንዱ ተሳትፎ ጥቅም እንዲጎበኘን የተሰባሰብን ከንቱዎች ሆነን ሳለ ከእኛ በላይ አሳቢ የሌለ ያህል መድረክ እንሞላለን...
ባቡራችን ወዴት እንደሚሄድ ግድ ስለማይሰጠን እንደ ተሳፋሪ አንጠይቅም... የየግል መነሻ እንጂ የጋራ መዳረሻ እንደሌለን እያወቅን ለተሳፋሪ ወንበር አንለቅም...
አንዳንዶቻችን ባቡሩ በልኩ እንዳይሄድ የምንጎትት ፉርጎ ነን... ሹፌሩ ልፍጠን ሲል 'እንዴት ተደርጎ!' እንላለን...
አንዳንዶቻችን በ locomotive ድክመት ፍጥነታችን የተገታ ምስኪናን ነን... አካሄዳችን ልክ አይደለም ስንል 'ዝም በሉ!' እንባላለን...
ከነዚህ የባስነው ደግሞ ለውጥ የማይሸተው Locomotive እና የማይሞቅ የማይበርደው Cargo ሆነን ሳለ እየሄድን ነው እያልን እንደነፋለን...
አይጓዙም እንዳንባል ስንንከላወስ እንታያለን፤ 'የት ደረሳችሁ?' ስንባል መልስ አጥተን እናፈጣለን...
ዥንጉርጉር ነን...
አንዳንዴ የተለያየ የሃሳብ ግዛት ውስጥ ካሉ ሰዎች ጋር የጋራ ሕልም ለማዋለድ የሚደክም ምስኪን መስሎ ይሰማኝና በኔዬ ተስፋ እቆርጣለሁ...
አንዳንዴ ከራሳቸው የሚበልጥ፣ ከዘመን ልኬታቸው የሚጠልቅ ሃገራዊ ሕልም ለማዋለድ የደከሙትን አስብና እበረታለሁ...
አንዳንዴ ደግሞ ካሳካሁት ይልቅ የማስበው መግዘፍ ያደክመኛል... ከሰራሁት ይልቅ ልሰራ የተገባው መብለጥ ያሳፍረኛል... መፍጠን በምችልበት ጊዜ መጎተቴ መሄድ በማልችልበት ወቅት ለተሰማኝ ድባቴ ምክንያት መሆኑን ማወቅ ያጸጽተኛል...
ከዚህ ሁሉ በላይ ግን...
.
.
.
ያለቦታዬ ቦታ ይዤ 'ተቀምጫለሁ' ማለቴ ያሳምመኛል...
____
[ካልተቋጨ የግል ማስታወሻ የተቆነጠረ...]
____
@bridgethoughts
.
.
.
በቋንቋ በኩል ስናጮልቅ...
.
.
.
እንደ እንግሊዝኛ ግን አምባገነን ቋንቋ አለ?... የምሬን እኮ ነው... ያልሆነውን ሁሉ አሁነን እንድንጠራው፣ የሌለውን አለህ እንድንለው የሚያስገድድ፣ የመጨረሻ አምባገነን ቋንቋ ነው...
ምሳሌ ልስጥህ፤
Book - ይሄ አሁን ምኑ ነው 'ቡክ' የሚመስለው?... ቋንቋው እኮ 'ቡ' የሚባል ፊደል የለውም... 'ክ' የሚል ፊደልም ወልዶ አያቅም... ጭራሽ እኮ አራት ፊደል ነው የያዘው... እንዴት ብሎ ነው በሁለት ድምጽ ብቻ የሚወከለው?... B ሁለት O ጠቅልሎ 'ቡ' እንዲባል፣ K ያለ ስሙ ስም ፈጥሮ 'ክ' እንዲሰኝ የፈቀደው ማን ነው?...
ሌላም ነገር አለ... 'BU' ለምሳሌ 'ቡ' ነኝ ሲል ብዙ ጊዜ ሰምተሃል... Bullet ሲደመጽ 'ቡሌት' የሚሆነው ለዚያ ነው... የሚገርመው ግን እኒሁ ፊደላት ዞር ብለው 'በ' ካልተባልን ሲሉም ገጥሞሃል... Butterfly እንዲሉ...
ነገሬ በቅጡ እንዲመጣልህ እነዚህን አራት ፊደላት ተመልከት - 'Ough'...
Enough - “ኢናፍ”፣ Though - “ዶ”፣ Tough - “ታፍ” እንዲሁም Through - “ትሩ” ተብሎ ይነበባል... አራቱም ቃላት አንድ ዓይነት የመጨረሻ ፊደል ቢኖራቸውም የሚነበቡት ግን በአራት የተለያየ ድምጽ ነው... ይህ የሚሆነው በምን ሂሳብ ነው ታዲያ - በአምባገነንነት ካልሆነ...
Read - ድሮ ድሮ “ሪድ” ብለን ነበር የምንለው... ዛሬ ደግሞ “ሬድ” ሆኗል... Red ምን ተብሎ ይሆን?... ፊደሉ አንድ ነው፣ ድምጹ ግን ተቀይሯል...
Lead - “ሊድ” ሲባል ብረት (ንጥረ ነገር ነው)... ራሱ Lead “ሌድ” ሲባል ደግሞ መመራት ይሆናል... ተመሳሳይ ፊደል፣ የተለያየ ትርጉም... Colonel በትክክሉ ሲነበብ “ኮሎኔል”
ነው፤ ልክ የሚያስብለው ግን “ከርነል”
ሲባል ነው... Queue አምስት ፊደል ያለው ቃል ነው... ሲደመጽ ግን አንድ ብቻ ይሆናል - “ኩ”... ሌሎቹ ፊደላት ምን ያደርጋሉ ታዲያ?...
አዎን...
This is not about English. This is about how agreement quietly replaces truth.
የማወራህ ስለ ፊደል አምባገነንነት አይደለም፣ ስለ ጅምላ ስምምነት እንጂ... ስለ ፊደል ድምጾች አይደለም፣ እውነትን እየደፈጠጠብን ስላለው መንጋነት እንጂ...
___
'ብዙሃን ልክ ናቸው' የሚል ስሁት መረዳት ፈጥረናል... 'ተለምዷል' የሚልን ስንፍና መሞገት ትተናል... እየሆነ ያለን ነገር በልኩ ለመመዘን ባለመፍቀድ ተረታ ተረቱን በ'ልክነት' ካባ አጎናጽፈናል... አንጠይቅም፣ አንፈትንም፣ አናናጽርም፣ ለአፍታ እንኳ ከተሰመረው ፈቅ አንልም...
ምሳሌዎቹን ካስተዋልካቸው እንግሊዝኛ ቋንቋ በራሱ እውነት አይፈጥርም... የቋንቋ ተጠቃሚዎቹ የኛ ስምምነት ነው እውነት የሚመስል ነገር የሚፈጥረው... በሌላ አገላለጽ አንድ ነገር ትክክል ስለሆነ አይደለም እንደ ትክክል የምንቀበለው፤ ስለተስማማንበት እንጂ...
ጭፍን ስምምነት ደግሞ በእውነት ላይ የሚጫን ጭቆና ነው... አስገድዶ ሃቂቃን ካድ የሚል አምባገነን ብቻ ነው... ሰዎች በአንድ ነገር ሲስማሙ
ያልሆነ ይሆናል...
የሌለ ይኖራል...
የተሳሳተው ትክክል ይባላል...
ስምምነት በፈጠረው ጫና ውስጥ ስትወድቅ ታዲያ ነገሩ ልክ አለመሆኑን ከመቀበል ይልቅ ልክነቱን ለማስረገጥ ብዙ ርቀት ትጓዛለህ... አገባብ፣ አናባቢ፣ ተናባቢ፣ ድምጸት ወዘተ የሚሉ ቅቦችን ትጠቀማለህ...
___
እንግዲህ በቋንቋው መስኮት ውስጥ ዓለሚቱን ተመልከታት... ያነበርነውን ስርዓት ገምግም... መስተጋብራችንን ሁሉ ፈትሽ... እውነት ብዙኅን ስለሚቀበሉት ቅጥፈት ሲባል በየመዳረሻው ትደፈጠጣለች... 'እነከሌ' ስላሉት ብቻ እውነትነቷን ታጣለች...
በዙሪያህ ያለው ሲስተም function የሚያደርገው በእውነት ነዳጅ አይደለም፣ በስምምነት ግዳጅ እንጂ... ብዙ ሰው የሚከተለው የፈተነውን አስተሳሰብ አይደለም፣ በደመነፍስ ያጸደቀውን እንጂ... በገባው ልክ እንዳይኖር ይሉኝታ የደፈቀውም ቀላል አይሆንም...
ስምምነት ጅምላዊነት ይጫነዋል... ከእውነት ፍለጋ ይልቅ ለስሜት ምላሽ ሰጪ ሆኖ መቅረብ ይቀናዋል... ስምምነቱ ስላለ ብቻ ልክነት፣ ብዙዎች ስለተቀበሉት ብቻ እውነትነት አለው ማለት ግን ያስቸግራል...
በሕግ ስርዓት ውስጥ ትናንት 'ልክ' የነበሩ ነገሮች ዛሬ 'ወንጀል' ሲሆኑ አይተሃል... የነገሩ ተፈጥሮ ስለተቀየረ ግን አይደለም - ሕግ አውጪዎች እንዲያ ስለተስማሙ እንጂ... (ፊደሎቹ ሳይቀየሩ ድምፃቸው እንደተቀየረው ማለት ነው)
በማህበረሰብ ውስጥ እያሉ እንደሌሉ የምንቆጥራቸው ብዙ ሰዎች አሉ... ከመኖራቸው እንገለገላለን - ግን አንሰማቸውም፤ ከድካማቸው እናተርፋለን - ፍላጎታቸውን ግን ከግምት ውስጥ አንከትም... የወል ስምምነቱ ያገለለውን ሁሉ በጸጥታ እናልፋለን... (ፊደሎቹ እያሉ Silent ተብለው እንደሚዘለሉት ማለት ነው)
ጊዜ
የእጃችን ላይ 'ሰዓት' የቀን ጅማሬና ፍፃሜን ይወስናል... የስራና የእረፍት 'ጊዜ' ገደብ ያበጃል... ግና የኛ አካል (body) ስለ ሰዓት አያውቅም... ጭራሽ ዩኒቨርሱ ላይ ጊዜ ኖሮ አያውቅም... ማሕበረሰቡ ጊዜን የሚለካው በስምምነት እንጂ በተሞክሮ አይደለም...
ድንበር
በካርታ ላይ የተጫሩ መስመሮች ሀገር ይሰራሉ... የአንድ እርምጃ ወደፊት ወይም ወደኋላ መሆን ሕጋዊነትና ሕገወጥነትን ይበይናል... ምድሪቱ ላይ እነዚያ መስመሮች የሉም... ስምምነት ግን አንብሯቸዋል...
ባለቤትነት
'ይህ መሬት የኔ ነው' ወይም 'ያ ወንዝ የነእከሌ ነው' ሲባል እናውቃለን፤ ብለንማል... የለየለት ደግሞ 'የወንዜ ልጅ' ብሎም ያዜማል... በተፈጥሮ ውስጥ ግን ስም ተለጥፎለት የተገኘ አንዳችም ነገር የለም... እንኳን 'የኛ' የምንለው ሊኖረን እኛም የኛ ሆነን አናውቅ... በመንጋ ስምምነት ግን ባለቤት ፈጥረናል...
ገንዘብ
አንዲት ቁራጭ ወረቀት በሕልውና ላይ ትወስናለች፣ መስተጋብር ትበይናለች፣ መደብ ትለያለች... እውነት ለመናገር ስምምነታችን ከፈጠረላት አቅም ነጥለን ካየናት ለመፃፊያ እንኳ የማንመርጣት ዥጉርጉር ወረቀት ናት... ዓለሚቱ ግን ጽድቅና ኩነኔዋን፣ ክፋትና ደግነቷን፣ ክብርና ውርደቷን ከዚሁ ወረቀት ትሰራለች...
ማዕረግ
ሰዎች ስለራሳቸው ከመናገራቸው በፊት title ስለነርሱ ይናገራል... የሆኑትን ከልሎ ያልሆኑትን ይሰብካል... ቃሉ ታዛዥ ይፈጥራል፣ ቃሉ አዛዥ ያደርጋል... ስለ ማዕረግ ስምምነት አዋቂና ታዋቂ ይምታታል... ማዕረግ የሌለው ጠቢብ በጊዜያዊ ስም ይዋጣል...
ትምህርት
የምስክር ወረቀት የብቃት ማረጋገጫ ይሆናል... የክላስ ውጤት የመረዳትን መጠን ይለካል... መማር ነጥብ ያስቆጥራል... ጥበብ ግን grade የላትም... ማሕበረሰብ በጠቢብ ልኬት ላይ ስምምነት የለውም...
ሌላም ብዙ ነገር...
___
መቋጫው ግን ምን መሰለህ?...
የያዙትን መፈተን፣ የደረሱበትን መጠየቅ፣ የተስማሙበትን መፈተሽ ብልህነት ነው... ከዚህ ሁሉ በላይ ግን ስለ ብዙሃን እምነት እውነትን እንዳልጨቆኗት ማረጋገጥ የአስተውሎት ከፍታ ነው...
ጸሐፊው እንዳለው...
“Whenever you find yourself on the side of the majority, it is time to pause and reflect.” ~ Mark Twain
___
@bridgethoughts
.
.
.
ለመያዝ የዘረጋ ካልቆመ፣ ለመጨበጥ የሰነዘረም ካልፈጠነ - በያዥና ተያዥ መሐል ፍላጎት ተፈትኗል...
.
.
.
ያልነበረ አይኖርም!!...
____
@bridgethoughts
ሰላም ወዳጆች...
___
መጽሔታችን ቀለም በሰዓቷ ከች ብላለች... ቅጽ ፩ ቁጥር ፮ እትምን በዚህ ሊንክ ታገኛላችሁ...
👇
@kelemofficial
ለምታውቋቸው ጋብዟት፤ ለጥበብ አፍቃሪያን ጠቁሟት...
ቻናሉን ተቀላቀሉ!!
ይህን ስለምታደርጉ እናመሰግናለን 🙏
.
.
.
'ለፈረሰ ቤት ብርሃን ምኑ ነው?' አትበይኝ፤ ከብርሃኑ የሚያተርፍ እስካለ ድረስ...
___
@bridgethoughts
ዶ/ር ጴሌ ዳሮታ ...
---
(ፍልስፍናን ከነነፃነቷ የኖራት፣ በልዩ ትወና የሰበካት አይረሴ ምሁር!)
-
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና ትምህርት ክፍል ረዳት ፕሮፌሰር የነበረውን የጴሌ ዳሮታን (ዶ/ር) ህልፈት የሰማ ከቀድሞ ተማሪዎቹ አንዱ የሆነው ‹‹አሳፍ ኃይሉ›› በማኅበራዊ ትስስር ገጹ ስለ ጴሌ (ዶ/ር) ካሰፈረው ረዘም ያለ የታሪክ ማስታወሻ በጥቂቱ ቀንጨብ አድርጌ ወደ እኔው ጥቂት ትዝታ ለማለፍ ወደድኹ፤
የዕውቁን የፍልስፍና መምህራችንን የዶ/ር ጴሌ ዳሮታን ህልፈት ሰማሁ። ከልብ አዝኜያለሁ።
በእርግጥ ፔሌ ቀጥታ የእኔ አስተማሪ ሆኖ ባያውቅም፣ ዝናውን በመስማት ጉዱን ለማየት ከጓደኞቼ ጋር ከአንድም ሁለት ቀን በእርሱ ሌክቸር ክፍለጊዜ ገብቼ ሎጂክን እንደ መደሰቻ ሽቶ ተርከፍክፌ ነው የወጣሁት ብል ማጋነን አይደለም!
ጴሌ በጣም ቀልደኛ ሰው ነበረ። ስሙን በእንግሊዝኛ "Pelle" ብሎ ይፅፍና፣ ዕድሜ ለእንግሊዝኛ "ጴ" የሚል ፊደል ስለሌለው ስሜን ከጴሌ ወደ ፔሌ ቀየረልኝ — በማለት ያሳቀንን አልረሳውም!!
--
የፍልስፍና መምህሩን ጴሌ ዳሮታ (ዶ/ር) በጨረፍታ በእኔው ትውስታ!!
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ፍልስፍናን ነፍስ ከዘሩበት ምሁራን መካከል በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀስ ነው፤ በ1990ዎቹ አዲስ አበባ ተማሪ በነበርንበት ጊዜ የፍልስፍና ትምህርት ክፍል መከፈቱ ስለነበር ከሌላ የትምህርት ክፍል/ዲፓርትመንት እያስፈቀድን ጴሌ የሚያስተምርበት ክፍል እንማር ነበር፡፡
አንድ ወቅት ላይ ስለ እውነታ /what is Reality? / በሚል አርእስት የግሪክ ፈላስፋዎችና ጥልቅ አሳቢዎች /Philosophers and Great Thinkers የተናገሩት/የጻፉትን ሐሳብ እያስተማረን ሳለ፤ አብዛኛውን ጊዜ እንደሚያደርገው በሌክቸሩ መካከል አንድ ጥያቄ ለእኛ ለተማሪዎች እንዲህ ሲል አነሳ፤
‹‹እውነት ለእናንተ ምንድን ነው? ማነው?››
ተማሪዎች እርስ በርስ እየተያየን ዝምታን አሰፈንን… ‹‹በሉ እንጂ አይዞአችሁ ባትመልሱት አያሰቅላችሁም እኮ!›› ሲል ለማደፋፋር ሞከረ፡፡ ከጥቂት አፍታ በኋላ ከፊት ተቀምጦ የነበረ ተማሪ ፍርሃትና ሥጋት በቀላቀለ ድምፀት፤
‹‹ለእኔ እውነት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው!›› ሲል መለሰ፡፡
ጴሌ፡- መላጣውን አሸት አሸት እያደረገ ‹‹አረ ባክህ… ተው እንጂ… ይሄኔ በእርሱ ዘመን ኖረህ ቢሆን ኖሮ ሲወገርና ሲሰቀል አንዱ ድንጋይ አቀባይ አንተ ትሆን ነበር?!›› ሲለው ክፍሉ በሣቅ አውካካ…
ከዚህ በፍርድ ወንበር ፊት ከተቀመጠው ከጲላጦስ፤ ‹‹እውነት ምንድ ነው?›› ጥያቄ ጋር በተያያዘ ጴሌ አንድ በገሃዱ ዓለም የሆነ ይሁን ወይም ራሱ የፈጠረው ይሁን ለጊዜው ትዝ ባይለኝም አንድ ታሪክ እንዲህ ሲል አወጋን፤
በናዚ ዘመን አይሁዶች በያሉበት እየታደኑ በመርዝ ጋዝ ሲያልቁ በነበረበት ክፉ ጊዜ አንዲት አይሁዳዊት እናት እና ልጇ ተደብቀው ይኖሩ ነበር፡፡ ይህቺ አይሁዳዊት እናት ለብቸኛው ልጇ እንዲህ እያለች ትነግረው/ታስተምረው ነበር፤
‹‹ልጄ እውነትን ውደድ፤ ሁሌም እውነት ተናገር!››
ታዲያ አንድ ወቅት ላይ የናዚ አሳሽ ወታደሮች በጥቆማ ወደ ቤታቸው ይመጣሉ፤ ወታደሮቹ በሩን ሲያንኳኩ ልጅ በሩን ይከፍታል፤ ልጁን በጥያቄ ያፋጥጡታል፤ ‹‹እዚህ ቤት ውስጥ አንተ ብቻ ነህ የምትኖረው?››
ልጅ ይመልሳል… ‹‹አይ እናቴም አለች ግን እናቴ በታችኛው ምሥጢራዊ ክፍል ውስጥ ነው ያለችው፤›› በማለት የናዚ ወታደሮችን እናቱ ወዳለችበት ይመራቸዋል፡፡
ወታደሮቹ እናቱን እና ልጁን ይዘዋቸው ሄዱ፤ የእናቲቱና የልጁ ዕጣ ፈንታ እንደ ወገኖቻቸው ሁሉ በመርዝ ጋዝ ጭስ ተቃጥሎ፣ ታፍኖና ተልብልቦ መሞት ሆነ…
ጴሌ፡- ታሪኩን ተርኮ ከጨረሰልን በኋላ የተለመደውን ጥያቄውን አስከተለ፤
‹‹ለመሆኑ ለዚህ የግፍ ሞት ተጠያቂው ማነው… እናት፣ ልጅ ወይስ የናዚ ወታደሮች?! ከመመለሳችሁ በፊት ጥቂት አስቡ ዝም ብላችሁ እንዳመጣላችሁ እንዳትመልሱ… ጎበዝ ‹‹F›› ለማግኘትም እኮ ትንሽ ማሰብ፤ ማሰላሰል ይጠይቃል…›› ዳግመኛ ክፍሉ በሳቅ ማዕበል ተናወጠ…
ጴሌ እንዲህ ዓይነት የፍልስፍና መምህር ነበር… ነፍሱ በጥበብ ፍቅር የነደደች…!!
ጴሌ ዳሮታ (ዶ/ር) ነፍስህ በሰላም ትረፍ!!
---
ጸሐፊ - ተረፈ ወርቁ (ወዳጄ ምስጋናዬ ይድረስህ) 🙏
—-
@bridgethoughts
.
.
.
የኔነሽ፣
የኔነሽ፣
የኔነሽ ይሏታል
እርሷም ደስ ይላታል
የሁሉ መሆን ግን ምን ያደርግላታል?
.
.
.
የሁሉ የሆነ - እንዳይሆን ለማንም
ሁሉ ዘንድ የሞቀ - እንዳይገኝ የትም፤
ጸሐይ ነግራናለች - በዘለለት ልሳን
ሰርክ አዲስ እንግዳ - እኛ እንጂ ያልነቃን፤
በጠዋት ፈገግታ
በእኩለ ቀን ዋዕይ
ከባን ብትውልም፣
ጽልመት ሲገማሸር አታስተማምንም።
___
@bridgethoughts
ሰላም ወዳጆች፤
ድልድይ - ቀለም ላይ አምደኛ ሆና ተከስታለች፤ ይህንን የጥበብ ብፌ ስጋብዛችሁ ደስ እያለኝ ነው...
___
ግቡ፣ Join አድርጉ፣ አዲሱን ቅጽ አንብቡ!!
___
ቀለም መጽሔት🗞️
ቅፅ 1 እትም 5
እያነበባቹህ ለወዳጅዎ ያጋሩ
ለሀሳብ አስተያየት
@KelemMagazine
Telegram 👇❤️
@kelemofficial
🔔 Before the Drums Beat Again 🔔
Once upon a time, there was no Ethiopia and Eritrea.
There were only brothers — children of the same highlands,
breathing the same wind that rises from the Red Sea
and settles on the mountains.
The rivers did not know borders.
The mothers spoke the same lullabies.
The sky covered us all — without a passport.
But then came the shadow of lines drawn on the earth —
names that separated hearts, flags that replaced embraces.
And in the name of these lines,
thousands of young men and women offered their blood to the soil.
Still, the soil cried — not for victory,
but for the innocence lost.
Years later, the world rejoiced when the two brothers met again —
smiles, handshakes, hope.
The world said, “At last, the Horn of Africa breathes again.”
You both promised peace,
and the earth, weary from the echo of guns, finally rested.
Our Prime Minister received the world’s peace prize —
but more importantly,
our people received the peace itself.
Seven years passed.
Yet now, we hear the sound of old drums beating again.
Excellencies,
Before those drums awaken the ghosts of yesterday, please —
sit and talk.
Sit not as leaders of separate lands,
but as brothers who share one ancient wound.
History has already buried too many sons.
Must we dig new graves for the same reason?
A sea is not worth a single mother’s tear.
A port is not worth the trembling of a child
who hears warplanes in the sky.
The world does not need another headline of sorrow from the Horn;
it needs the light of wisdom from its cradle.
Yes — Ethiopia needs a gate to the sea.
And yes — Eritrea needs her sovereignty respected.
But more than that, both need each other.
The sea and the highlands are not enemies;
they complete each other —
like breath and heartbeat.
If you two meet,
not to debate, but to listen —
the Red Sea will calm its waves.
Trade will flow, families will unite,
and the wounds of decades will begin to heal.
But if the guns speak again,
no one will win —
except those who sell the bullets.
Please, for the sake of history yet to be written,
for the mothers who have already buried too much,
for the youth who dream of life, not war —
Sit and talk.
Let wisdom be your weapon.
Let love be your strategy.
Let peace be your legacy.
The Horn does not need heroes of war anymore.
It needs fathers of peace.
🕊️ May reason rise above rage,
and may love remember what history forgets.
____
@bridgethoughts
.
.
.
ሰዎች በአንድም በሌላም መንገድ ሊጎዱህ ይችላሉ፤ የዝቅተኝነት ስሜት እንደሚያንገላታው ሰው ግን የሚያሳምምህ አይኖርም።
___
@bridgethoughts
መንደርደሪያ...
___
✔️የምንተቸው የማናደርገውን ነው ወይስ ዕድሉን ብናገኝ የማንዘለውን?... ✔️
ክህደት፣ ኩራት፣ ንቀት፣ ህሊናቢስነት ወዘተ፣ የየራሳቸው ብዙ ጥቅስ፣ ብዙ አባባል፣ ብዙ ምሳሌና ብዙ ተረቶች አሉዋቸው... ትናንት ወላጆቻችን በቡና ላይ ሐሜት ይኖሩት ነበር... ዛሬ ደግሞ በዘመን መድረክ እኛ እየኖርነው ነው...
ሰው ማማት ደስ ስለሚል የሐሜት አድናቂው ብዙ ነው፤ ሁሉም አንገቱን ይነቀንቃል፣ 'ልክ ነህ፣ ልክ ነሽ' ይላል... Like share repost ያደርጋል...
ሁሉ ተቺ ከሆነ - ማነው 'ንጹህ' ሰው?... ሰው ሁሉ ችግር ካለበት ታዲያ ልክነትን እንዴት አወቅነው?... በጎነት ከሌሎች ብቻ የምንጠብቀው ከሆነ እኛ መች ነው የምንኖረው?...
ድራማው በአባባል የተሞላ ነው... ቲክቶክ በዚህ የሰለጠነ ነው... ሬዲዮው፣ ቲቪው፣ ጋዜጣው፣ ውይይቱ፣ ጓደኝነቱ... ሁሉም እየተነሳ የሰው ልጅ እንዲህ ነው፣ የሰው ልጅ እንዲያ ነው በማለት የሚበይን ነው...
ለመሆኑ እኛ ምንድን ነን?... ሰው አይደለንም እንዴ?...
የሆነ ሰው እንዲህ ሲል 'ደስ የሚለን፣ አሃ፣ ልክ ነው እኮ...' ምናምን የሚያሰኘን በተወቃሾቹ ዝርዝር ውስጥ እራሳችንን እያየን ነው?... የወቃሹንስ እንዲያውነት እያመንን ነው?... የሰው ልጅ በሙሉ እንዲህ ከሆነ ሰውነት አብቅቶለታል ማለት ነው?... ታዲያ ምን እንሁን?...
.
.
.
እንዳልኳችሁ ነው...
ሁላችንም መተቸት እንወዳለን... [እርግጥ በኑሮአችን ውስጥ ትችት ቀላሉ ተግባር ነው... የማቅናት ዓላማ የሌለው አስተያየት ዕውቀትም ሆነ ልምድ አይፈልግም...] እናም፣ ሁሏንም ነገር እናብጠለጥላለን... ጓደኝነትን፣ ማህበራዊ ግንኙነትንና የሰው ልጅ ምንነትን በየቀኑ በሂስ ሚዛን ላይ እናስቀምጣለን... "ሰው ተበላሸ፣ ክህደት በዛ፣ ንቀት ነገሰ" ወዘተ እንላለን... ነገር ግን ይህ የምንተቸው "ክፋት" የት ነው ያለው?... ከእኛ ውጭ ወይስ በእኛም ውስጥ?...
ነገሩን ከፈትፈት ለማድረግ - "ሰው እኮ!" የሚለው ድምጸታችን ውስጥ ሰውነታችን አለ ወይ?... ነው ወይስ ራሳችንን ከዓለም ንጡል አድርገን ነው የምናስበው?...
[ይህንን ሃሳብ በቅጡ ለማንጸር እንዲያስችለን የተለያዩ መነጽሮችን እንዋስ...]
⬜️ ሚስቲሲዝም (Oneness)
በተማላዮች (Mysticism) እይታ፣ ዩኒቨርሱ አንድ ነው... "እኔ" እና "ሌላው" የሚባል መስመር፣ እዚህና እዚያ የሚባል ድንበር ወይም ደግሞ ዓይነታዊ (ሰው፣ እንስሳ፣ ተራራ፣ ሰማይ... ወዘተ) የሚል ተናጥሎ የለም... ስለዚህም ሌላውን ስንተች፣ በእውነቱ የምንተቸው የራሳችንን ነጸብራቅ ነው...
'The eye with which I see God is the same eye with which God sees me." — Meister Eckhart
"In quantum physics, the observer creates the reality." — Amit Goswami
“Now, there is one thing you might have noticed I don’t complain about: politicians. Everybody complains about politicians. Everybody says they suck. Well, where do people think these politicians come from? They don’t fall out of the sky. They don’t pass through a membrane from another reality… it’s what our system produces: Garbage in Garbage out. If you have selfish, ignorant citizens you’re going to get selfish & ignorant leaders…” ~ George Carlin
የካንቲኗ ውበት - የሁሉ እናት
_
[የንጹህ ልብ ማስታወሻ]
[Tip የማይወዱ ሰዎች ይህን ጽሑፍ እንዲያነቡ አይመከርም]
____
መኪናው ወደፊት እየተወነጨፈ ልቤን ወደኋላ የሚስበው ነገር ምን ይሆን?... በመድረስ ጉጉቴና በተጓዥ ልቤ መሃል ተሰንቅሮ የሚቆረቁረኝስ ምንድነው?...
የእኛ ነገር - መገናኘት ደግሞ መለያየት፣ መተዋወቅ ደግሞ እልም ብሎ መራቅ፣ መግባባት ደግሞ እስኪረሳሱ መጥፋት...
በሕይወት አንድ ቀን ጉዳይ ሰበብ ሆኖ ሰዎች ወደ ልባችን ጓዳ ይገባሉ... በሌላ አንድ ቀን መራቅ ምክንያት ሆኖ ከልቡናችን ሸራ ይደበዝዛሉ...
እያንዳንዱን የሕይወት አፍታ ከናቅን፣ እያንዳንዲቷን በጎነት ቸል ካልን ሕላዌ ጣዕም አልባ ትሆናለች... ካስተዋልን ግና ከዕለት መገረም የሚሻገር የትዝታ ስንቅ እንፈጥራለን... ለሌሎች የሚነገር አብነት እናቆያለን...
____
በኮይሻ የኮንስትራክሽን ሁዳድ...
ማሽኖች ሰርክ በሚያጓሩበት፣ ጸሐይ በወበቅ በምታነድበት፣ በተራሮች መሃል፣ በጥቅጥቅ ጫካ ውስጥ - አንድ ልዩ ኃይል አየሁ...
ይህ ኃይል ከተርባይኖች የሚመነጭ አይደለም... ይህ ኃይል በኬብል ውስጥ የሚፈስ አይደለም... ይህ ኃይል - በጸጥታ፣ በእርጋታ፣ በትጋት ከአንዲት ሽርጥ ለባሽ ሴት እጅ ላይ የሚፈስ ኃይል ነው...
እርሷ ሼፍ ናት... ግና ቃሉ ለእርሷ ሲሆን በቂ አይደለም... ኮካ ይሏታል ባልደረቦችዋ... ሁነኛ ስምዋ ፋንታነሽ ነው... የኮይሻ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት የሰራተኞች ካፌ ሼፍ ናት... በአጭር ቆይታዬ ከአካል ግዝፈት ማዶ ያስተዋልኩዋት እናት!!...
___
እስኪ ልጠይቃችሁ...
የቅን ሰውን ልብ ለማየት ምን ያህል ጊዜ ይወስዳል?... የዋህ ልብን ለመረዳት ስንት ዓመት ይበቃል?... ርህራሔን፣ ፍቅርን፣ ትህትናን ለመገንዘብ ስንት ወር ያስጠብቃል?... ስንት ሳምንት? ስንት ቀን? ስንት ደቂቃ?...
አንዳንዴ - ቅጽበት የብዙ አስርት ዓመታትን እውነት ይገልፃል... ሌላ ጊዜ - ቀጭን አፍታ በከረመ ዕውቀት የማይገባ ሃቂቃን ያሰርፃል... ድንገት ልቦች ይገቡሃል፣ ድንገት ስሜት ይሸትሃል፣ ድንገት መንፈስ ይጋባሃል...
በዚያ ጨረፍታ እናትነት፣ በዚያች ቅጽበት ርህራሔ፣ በዚያች አፍታ የስብዕና ጥልቀት ይታይሃል...
___
ኮይሻ የቆየሁት ጥቂት ቀን ነው ብያችሁ ነበር - አዎን አራት ቀን ብቻ... እርሷ ውስጥ ያየሁት ቀለም ግን ዕድሜ ልኬን የማውቃት ያህል እንዲሰማኝ አድርጓል...
ካፌ ተቀምጠህ ቤትህ እንዳለህ ተሰምቶሃል?... ምግብ ጣት አስቆርጥሞ የእናት እጅ አስታውሶሃል?... የመስተንግዶ ልዩነት ክብር እንዲሰማህ አድርጓል?... እንግዲያው አንዳች ልዩ ነገር በዚያ ነበር ማለት ነው... ምናልባት አንዲት ምርጥ ነፍስ እዚያ ነበረች ማለት ነው...
[በነገራችን ላይ...]
Tip የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል የተፈጠረው በኢትዮጵያ ቡና ምክንያት ነው ይባላል... አንድ አውሮፓዊ በሃገሩ ከሚገኝ ካፌ ውስጥ ቡና አዝዞ ሲጠጣ፣ የጣዕሙ ለዛ የተለየ ስሜት ይፈጥርበታል፤ ከዚያ በፊት ተመሳሳይ ቡና ጠጥቶ አያውቅም ነበርና ስሜቱን የሚገልጽበት መንገድ ማሰቡ አልቀረም...
እናም የቡናውን ክፍያ ሲፈጽም ከዋጋው በላይ የሆነ ሂሳብ አስቀመጠ... ወዲያው አስተናጋጇ መጥታ፣
'ጌታዬ፣ መክፈል ያለብዎ ይህን ያህል ብቻ ነው' ትለዋለች
'አውቃለሁ - ትርፉ Tip ነው' አላት፤
'አልገባኝም'
'ሁሌም ተመሳሳይ አገልግሎት እንድታቀርቡ ማበረታቻ ነው - [To Insure Promptness]' አላት... ከዚህ ጊዜ በኋላ Tip መስጠት ባሕል ሆነ... ቃሉም በአጽሮት መንገድ የቋንቋችን አካል መሆን ጀመረ...
እንግዲህ ይህ ጽሑፍ ባልተጠበቀ ሁኔታ ለተገኘ የላቀ መስተንግዶ የቀረበ የምስጋና Tip ነው...
____
(ይቀጥላል...)
🗣️
.
.
.
... ከዚያ እስከዚህ ድረስ እቡይ ዘመን ተደንብቶብናል። አስማታዊ ዓለም ውስጥ፣ ተሳትፏችን እንደባህር ትል፣ ፈልቶ በቀዘቀዘ የድንጋይ ኩርፍርፍ ውስጥ፣ ፈሪ ልቡና እያስታመምን ሌላ ዘመን መጠበቅ ሆነ፡፡ ባለብዙ ደጃፍ ጉሮኖ በመፍጠር እራስን መታደጊያ የአይጥ ደመነፍስ እንኳ የለንም…
... መነሻ ትናንታችንና መድረሻ ነገአችን እንደ እትብታችን የተቀበረበት ጠፍቶን ዛሬአችን ላይ መተራመስ የማይለወጥ ዕጣፈንታችን ሆኗል፡፡
... የተበጠሰ ጣት እንደ እንሽላሊት መሸሸጊያ ሲያስስ የመመልከት ያህል ህልውና ተአምር ናት፡፡ እንደገና ሌላ ጣት... ከጣት ላይ ሌላ ጣት፣…ጣት፣ ጣት፣ ጣት… ከምንጩ የተጨለፈ ሌላ ምንጭ… ነባሩን ምንጭ ያድበሰበሰ ሐሰተኛ ምንጭ በተተኪው ሌላ ምንጭ ይረሳሳል።
.
.
.
____
ዓለማየሁ ገላጋይ
"ሐሰተኛው በእምነት ስም"
____
@bridgethoughts
.
.
.
⚡️ የለቅሶ ቤት ምስር የሚጣፍጥህ ቤትህ እስኪሰራ ድረስ ነው።⚡️
___
@bridgethoughts
.
.
.
ነገሩ...
በጭቃ የተሞላውን 100 ሜትር መንገድ በጥንቃቄ ስትጓዝ ቆይታ ዘጠና ስምንተኛው ላይ ስትደርስ ያዳለጣትን ሴት ታሪክ ይመስላል...
ይህች ሴት ተነስቶ ለመሄድ አልሰነፈችም... ውጥኗን ለመጨረስም አልደከመችም...
ተመልካቹ ግን ክረምት በመጣ ቁጥር የሚያስታውሳት ጠንክራ ባለፈችው አስቸጋሪ የመንገዱ ክፍል ሳይሆን አዳልጧት ሸርተት ባለችበት የጉዞዋ መቋጫ ነው...
ይገርማል...
ወሬውን ከሚያወሩት ሰዎች ውስጥ ብዙዎቹ መውደቅን ፈርተው መንገድ መቀየራቸውን አብረው አያነሱም...
___
@bridgethoughts
እየራራን
(በእውቀቱ ስዩም)
ዛሬ በስሱ እንድሰብካችሁ ፍቀዱልኝ!
ከአውሮፓ ከተሞች በአንዱ እግር ከጣለህ የሆነ ነገር ታያለህ፤ መንገድ ላይ ስትሄድ የደላቸው የጠገቡ ርግቦች ያጋጥሙሀል’፤ አጠገባቸው መድረስህን አውቀው መንገድ አይለቁልህም፤ ከመጤፍ ሳይቆጥሩህ፥ ለቀማቸውን ወይም ጨዋታቸውን ይቀጥላሉ፤ እንዳትረግጣቸው ርምጃህን ቆጥበህ ለመራመድ ትገደዳለህ፤
‘ቅዲስቲቱ ምድር’ ላይ ነህ፤ አንዲት ወፍ ከከረጢት ያመለጠ እህል እየለቀመች ነው፤ ድንገት ባቅራቢያው ዳናህን ከሰማች ብድግ ብላ ወደ እንጦጦ ብሄራዊ ፓርክ ታፈገፍጋለች፤ በወፎች ዓይን ስንታይ ጭራቆች ነን፤ ግን ያለ ምክንያት ነው?...
አንድ ባለቤት አልባ ውሻ ባጠገቡ ካለፍህ ሽምቅቅ ብሎ ገለል ይላል፤ ይመግቡኛል ብሎ ሳይሆን ይደበድቡኛል ብሎ እንደሚያስብ ግልጥ ነው ፤ በከተማችን የዕለት ዱላውን ሳይቀበል የሚውል ውሻ የለም፤ ድሮ ሰዎች የጎዳና ውሻ የሚደበድቡት “ሊጣችንን ደፋብን፣ ከቅርጫው መደብ ላይ አንድ ጎድን መነተፈብን” በሚል ሰበብ ነበር፤ አሁን አሁን ያለ ሰበብ ውሻና ድመት የሚነርት ነዋሪ ጥቂት አይደለም፤ ለመዝናናት ወይም የቆረፈደ ክንዱን ለማፍታት ውሻ የሚደበድብ አለ፤ ረሀቡን በአንቅልፍ ለማሳለፍ የተኛውን ውሻ ከመንገድ አፈንግጦ በወጣ ኮብል ድንጋይ የሚወግር አይጠፋም፤
በቀደም አንዱ ከሱቅ በር ላይ ተጎልቶ የሚቅም ጎረምሳ ባንድ ምስኪን ውሻ ላይ ድንጋይ ወረወረበት፤ ውሻው ከድንጋዩ ለማምለጥ ደመነፍሱን አስፋልት ለማቋረጥ ሲሞክር ከላይ የመጣ ታክሲ በጎማው እግሩን ዳጠው! ውሻው እያነከሰ ያለቀሰው ለቅሶ!...
ካዲስአባ እምብርት እየራቅን ስንሄድ እቃ የሚያጉዋጉዙ ጋሪዎችን እናገኛለን፤ አንድ የጠወለገ ፈረስ ትልልቅ ጎማ ያለው ጋሪ ለመጎተት የሞት የሽረቱን ሲፍጨረጨር ታያለሽ፤ በጋሪው መዓት የስሚንቶ ከረጢት ተከምሯል፤ ከስሚንቶው በተረፈው ቦታ ቡልኬት ተገጥግጦበታል፤ በዚያ ላይ ጋሪ ነጂው እንደ ፈርኦን ተኮፍሶ ፈረሱን በጅራፍ ይጠብሰዋል፤
በእንስሳት መገልገል አንድ ነገር ነው፤ በአንስሳት አለምክንያት መጨከን ሌላ ነገር ነው፤ የከተማው አስተዳደር የጋማ ፈረሶችን ያላግባብ የሚጨኑ፥ በግልጋሎታቸው ሳይሆን በስቃያቸው የሚደሰቱ ሰዎችን መቅጣት አለበት፤
ለመኖር እንስሳትን መግደል አለብን፤ ይህ የህይወት አንድ አሳዛኝ ግን አይቀሬ ገጽታ ነው፤ ከዚያ ባሻገር ለእንስሳት ርህራሄ የማሳየት ዝንባሌም አናጣም፤ የኢትዮጵያ ባህል ባንድ ገጹ ለእንስሳት መራራትን ያስተምራል፤ ድንግል ማርያም የተጠማ ውሻ እንዳጠጣች ሲነገረን አድገናል፤ ያገራችን የባላባት ወግ ስለ ዝሆን ገዳዮች ጀብድ ባድናቆት የሚተርከውን ያህል ስለ “ቆቅ ማሪ አቦየ”ም ይተርካል፤
እኒህ አቦየ የዳግማይ ምኒልክ አያት የንጉስ ሳህለስላሴ አማች ነበሩ፤ ባንድ ወቅት አንድ ባላገር ቆቅ አጥምዶ እጅመንሻ አመጣላቸው፤ ለባላገሩ የሚገባውን ከሰጡት በሁዋላ ወደ መኝታ ቤታቸው መስኮት ተራመዱ፤ ማጀት ውስጥ ገረዶቻቸው ቢላዋ እየሳሉ ነው፤ አቦየ ቆቂቱን መስኮት ላይ አስቀመጡና “ደህና ሰንብቺ” አሉዋት፤ ወደ መጣችበት በረረች፤
ያገሩ ሰው ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አቦየን “ ቆቅ ማሪ አቦየ” ብሎ ባድናቆት ይጠራቸው ጀመር!
አለምክንያት በእንስሳት ላይ የመጨከንን ልማድ አስወግደን የመንፈስ ስልጣኔ ያለን ህዝቦች መሆናችንን እናሳይ!
--
@bridgethoughts
.
.
.
Responsibility [Response + Ability]
.
.
.
ሰው ፈሪ ሲሆን መሆን የሌለበት ብዙ ነገር ሊኖር ይችላል፤ የስራ ኃላፊ አለመሆንን የሚስተካከል አስተዋይነት ግን አይኖርም...
ፈሪ ሆነህ ውሳኔ በሚፈልግ ወንበር ላይ መቀመጥ ኃላፊነት ለወሰድክበት ጉዳይ የቁም ሞት ግድ ማጣት ብቻ ሳይሆን ለከት አልባ ራስ ወዳድነትም ነው...
ስሙን ሽተህ፣ ኃላፊነቱን ግን ሸሽተህ እንዴት ይቻላል?... ክንውኑን ፈልገህ፣ መከወኑን ግን ገፍተህ እንዴት ይሆናል?...
የምልህ...
እስከመቼ ነው ከውሳኔ ጋር ሌባና ፖሊስ የምትጫወተው?...
ወይ ውረድ! ወይ ፍረድ...
በየቀኑ ዕዳህን ለሌሎች እየገፋህ መሹለክለክ አትችልም... አንተ የሸሸኸውን ኃላፊነት ሌሎች እንዲወጡት በማድረግ ተራ ብልጣብልጥነት መዝለቅም ብልህ እያስብልም...
ምንድነው እንዲህ መንቀጥቀጥ?... ምንድነው እንዲህ መራድ?... እንዴ... ትንሽ እንኳ ደፈር በል እንጂ ጎበዝ... Risk ውሰድ...
"The biggest risk is not taking any risk... In a world that is changing really quickly, the only strategy that is guaranteed to fail is not taking risks." ~ M. Zuckerberg
.
.
.
አንዳንድ ሲስተም ግን ይገርመኛል... ያንተ ዓይነቱን ለመሸከም ምንም አያቅማማም... ውሳኔህን የሚፈልጉ ሁሉንም ጉዳዮች ተጠያቂነት በመፍራት ስም እያሸሸህ ተድበስብሰህ ብትኖርም ምንም እርምጃ አይወስድብህም...
*ምን ጀምረህ - ምን ፈጸምክ?...*
*አንተ ነክተኸው ምን ከዳር ደረሰ?...*
*ባንተ ነገር ማወሳሰብ ስንቱ ነገር ተፋረሰ?...*
*ባንተ ጠርጣሪ ልብ ስንት ዕቅድ ፈረሰ?...*
[ማንም አይጠይቅህም... ያ - ነው ችግሩ...]
ይህ ግን ከሕሊና ወቀሳ አያስጥልህም... የጊዜ ጉዳይ ነው... ቢያንስ በሽኮኮ አያያዝህ እየሞቱ ያሉ ነገሮች በአደባባይ ያሰጡሃል... 'ስንት ነገር እጅህ ላይ ሞተ?' ይሉሃል...
ደግሞ አለመወሰንም የሚያስጠይቅ ሆኖ ይመጣል እኮ... ቀሽም ሲስተም ስለተሸከመህ ሲስተሙን የሚገፋ ዘመን አይመጣም ብለህ አታስብ...
አነሰም በዛ በዙሪያህ ውሳኔ የሚሰጡ ሰዎች አሉ... ምንም ሲሆኑ አላየንም... በጤነኛ አዕምሮ ካሰብከው አንተ ስታደርገው የሚያስጠይቅ ሌሎች ሲከውኑት የሚያስፈነድቅ የሚባል ነገር የለም...
[አንዳንድ ሁኔታህ ሲታይ ግን፣ የሆነ ጥግ ተቀምጦ እስክትፎርሽ የሚጠብቅህ ሰው ያለ ነው የሚመስለው...]
የአንድ ነገር የልክነትና ስህተት ዳሩ የሚመዘነው በተሰጠህ ኃላፊነት ወሰን እንጂ በማን መሆንህ ሚዛን አይደለም...
ሆን ብለህ ካጠፋህ ትጠየቃለህ፣ ካለማህም እሰየው... Period!!
ወትሮስ Position የ Responsibility እና Accountability ድምር ካልሆነ ምን ሊሆን ነው?...
___
እባክህ...
ወይ ከፍርሃት ቆፈንህ ተላቀቅ - ወይ ወንበሩን ልቀቅ!!...
___
“The coward asks the question, Is it safe? The leader asks the question, Is it right?” ~ James Freeman Clarke
___
@bridgethoughts
The Fallen Lineman
.
.
.
ለእርሱ...
ስሙን ከማወቃችን በፊት፣ ያኔ ድሮ - ራሱን ለመስመር ለሰጠው... ከተሞች ባንቀላፉበት ቀዝቃዛ ለሊት በምድሪቱ ለተመላለሰው... በሚንቀለቀል ነበልባል ሙቀት ከምሰሶ ጋር ለታከከው... ብናኝ ካፈነው ንፋስ ጋር ታግሎ ታወር ለደመረው... ፒንሳ፣ ሽቦ፣ ቀበቶና ስታፌ ታጥቆ ብርሃን ለሚያዋልደው...
ለእርሱ...
በጊዜ ቤት መግባት ለማይሆንለት... ልጆቹን በንቃት ማግኘት ለሚናፍቀው... እንቅልፍ ሲጥላቸው ተኝተው፣ ሲበረቱ ከበር ጠብቀው - አቧራ የጠገበ ጫማውን፣ በላብ የተላቆጠ ልብሱን፣ ድካም ያዛለው ገላውን እያዩ ለሚያዝኑለት...
[ግን ደግሞ ለማያዝኑበት...]
ብርሃን ለናፈቀ ሕዝብ የሚደርስ አባት እንዳላቸው ስለሚያውቁ ለሚኮሩበት... ለእርሱ!!
__
[ከተማው ሲፈካ ሰዎች ይደሰታሉ... ጨለማው ሲገፈፍ እልፎች ይረካሉ...]
የመጨረሻዋን ምሰሶ በዝናብ እየተደበደበ የወጣትን ሰው ግን አያውቁትም...
የመጨረሻዋን ገመድ በሃሩር እየደበነ የሳባትን ሰው ግን አያውቁትም...
ለዚያች ከተማ ድምቀት አካሉን የገበረውን ሰው ግን አያውቁትም...
ለዚያች አምፑል ብርሃን ሕልውናውን ያጣውን ሰው ግን አያውቁትም...
[ቢያውቁትም አበጀህ አይሉትም... ይልቁን ለስድብ፣ ለውርደት፣ ለነቀፋ የሚቀላቸው ሰው ነው...]
__
ሕዝቤ መብራት ሲጠፋ ጠብቆ 'ዓይናችሁ ይጥፋ!' ለማለት ብርቱ ነው...
ግና...
ለጥቂት የሳቱት የታወር ብረት፣ ዝናብ አርሶት ያዳለጠ መሬት፣ የተወረወረ የሽቦ ብጥሳት፣ የተለኮሰ የመስመር እሳት - የስንቱን ሕይወት ቀጥፎ ብርሃኑ እንደተገኘ አያውቅም...
ወፍ ሳይጮህ፣ ፀሐይ ሳትወጣ ከቤቱ የወጣ - ግና በበሮቹ መሃል መመለስ ያልቻለ ባሏን አስባ ሚስት እንዴት እንደምታነባ አያውቅም...
የአባት ኮቴ፣ የጎብኚ ድምጽ፣ የዘመድ ሰላምታ ሲርቅ - ልጆች እንዴት እንደሚሆኑ አይገምትም...
[ሕዝብ አንድ ነገር ብቻ ያውቃል... ከሆዳቸው በላይ ሕልም የሌላቸውን ከንቱዎች፣ ከድሆች አፍ መንጠቅ የማይቆረቁራቸውን ነጣቂዎች፣ ለማገልገል የተሰጣቸውን ዕድል የሚገለገሉበት ነውረኞች...]
_
ይህን የወደቀ ሰውን ጓዳ ግን አያውቁም...
__
[እርግጥ ነው -ይህ ሰው በስጋ አልፏል...]
እያንዳንዲቷ ደማቅ አምፑል ግን ደማቅ ትግሉን ትናገራለች...
[እርግጥ ነው - አንደበቱ በሞት ክንድ ተሸብቧል...]
እያንዳንዷ መስመር ግን የሕይወት መስዋዕትነቱን ትመሰክራለች...
[እርግጥ ነው -ስምና ታሪኩ ተዘንግቷል...]
በእያንዳንዱ ታወር የምትፈሰው ኢነርጂ ግን ቦይ የቀደደላትን እጅ ታስታውሳለች...
__
እርሱ የመስመር ሰራተኛ ብቻ አልነበረም...
የማይታይ የሃገር ዋልታ፣ የሰርክ ድምቀቷ ባለውለታ እንጂ...
እርሱ ቴክኒሺያን ብቻ አልነበረም...
የምድሪቱን ጭለማ በብርሃን ስለት የሚገልጥ መምህር፣ አጥንትና ወዙን ለሃገሩ የሰጠ ወታደርም እንጂ...
__
ዛሬ ይህን ብርቱ ሰው አሰብኩ!!...
[በእርሱም ውስጥ...]
እያንዳንዱን ምሰሶ ያለፍርሃት የሚወጣ፣ እያንዳንዱን ታወር በልበ ሙሉነት የሚረግጥ፣ ከእያንዳንዱ ሽቦ ብርሃን የሚያፈስ ቋሚውን የመስመር ሰው አወደስኩ...
___
ክብር ለወደቀው የመስመር ሰው!!...
የወጣባቸው ምሰሶዎች ዛሬም እንደቆሙ ነው...
የጠገናቸው መስመሮች የብርሃን ጅረት እያፈሰሱ ነው...
በእጁ የዳሰሳቸው አምፑሎች መደብርና መንደሩን እያደመቁ ነው...
እርሱ በአካል ባይኖርም የስራው ፍሬ በዙሪያችን እንደከበበን ይኖራል...
_
ይህ ሰው ዝነኛ አልነበረም - አይታወስም...
ሀብታም አልነበረም - በስሙ ሐውልት የለም...
ሆኖም...
[ሃገሩ በግብሩ ቀና እንድትል የሚያደርግ ያልተዘመረለት ጀግና ነው...]
___
ይህ ድምጽ ለእርሱ ለወደቀው ለመስመር ሰው የቀረበ አኮቴት ነው...
___
[ጓዴ ነፍስህ በሰላም ትረፍ]
___
@bridgethoughts
.
.
.
ሳንወሻሽ 😄
አንዳንድ ጉዳዮች ላይ ምን ያህል 'ሰነፍ' ናችሁ?...
___
@bridgethoughts
.
.
.
"Let him who is without sin among you be the first to throw a stone at her." ~ Jesus
__
ፍርድ እውቀት አይጠይቅም... ማንም ሰው ላይ መፍረድ ቀላል ነው... የሞራል ጥያቄ ግን አለው... 'አንተ ማን ሆነህ ነው ሌላው ላይ ጣት የምትቀስረው?' የሚያስብል...
የ blame shift ጨዋታ በጣም ያስተዛዝባል... 'ከደሙ ንጹህ ነኝ' ክህደት በጣም ያሳቅቃል... 'የወደቀ እንጨት' ላይ ምሳር መጠቅጠቅ የባለ እጁን ቁሸት አይከልልም... 'እነ እከሌ' የማለት ድፍረት የእኔታን በደል አይፍቅም...
ሁላችንም ቤት ጉዶች አሉ... ወይ እስኪመቸን የምንጠብቅ 'አድፋጮች'፣ አልያም ነጥቀን የምንሰጋ 'ድንጉጦች' ነን... ይህን መካድ አይቻልም...
አዎን...
እስክንያዝ እንጂ ሁላችንም የሰረቅነው አለን... ስላልተመቸን እንጂ ልንዘርፍ የምናደባለት አለን... ይህ የሚዋሽ አይደለም...
በነገራችን ላይ ሌሎች ላይ የምንቀስራት ጣት ስሟ 'ሌባ ጣት' ይባላል...
___
ሃበሻ ጥሩ ብሂል አለችው...
"ስራው ያውጣው" የምትል...
በምሳሌዋ ውስጥ... በግል - ከፍርድ የመቆጠብ ትህትና፣ ለሌሎች - ከተግባር የሚወለድ አርነት፣ ለሁሉም - በጥፋት ልክ የመዳኘት ፍትሕ ተዛንቆ ይታያል...
አዎን... ሁሉም ስራው ያውጣው!!
__
እጆቹን በማንፃት ላይ የተጠመደ ድንጋይ ይወረውር ዘንድ አይቻለውም...
___
@bridgethoughts
.
.
.
"ምንአገባኝ?" ብሎ መተው እኮ ይቻላል...
"ማንን ነው የሚያገባው ታዲያ?" ቢሉን መልስ የለንም እንጂ...
__
የገጠመን ፈተና ይህ ነው... ብዙ ሰዎች ብዙ ነገር አያገባቸውም...
ለዚህ ነው - ሃገር የጥቂት ትጉሃን መዋጮ ውጤት ነች ለማለት የምደፍረው... ብዙሃኑ ነገር ዓለሙን እኒሁ ጥቂቶች ላይ ጥሎ 'ጥቅሙን' ብቻ የሚያሳድድ ነው...
__
በተገኘህበት ቦታ - 'መገኘትህን' የሚናገር አንዳች ቁምነገር ካልተውክ መኖርህ ከቁጥርነት አልዘለለም ነበር ማለት ነው...
__
@bridgethoughts
.
.
.
ሁሉንም አታወራም አይደል?... ሁሉን ከሁሉ ጋር አትካፈልም...
አንዳንዴ...
በግል ጉባኤህ፣ በልብ ሽሽግህ፣ በነፍስያህ ለዛ፣ ካዘመመ ጎጆህ ታዛ - ብቻህን ቆዝመህ የምታንሾካሹከው ጉዳይ ይኖርሃል...
ደግሞስ ሰው ሁሉ በየቤቱ በራሱ ድካም እየደቀቀ፣ በግሉ ሃሳብ እያለቀ፣ በዕጣፈንታው ህመም ታስሮ፣ በራስ ፈተና ተቸንክሮ - ጉስቁልቁል እያለ ምን ብለህ የኔን ብቻ ስማ ትለዋለህ?...
ከመከራህ መከራዬ ይልቃል ነው?...
ከስቀትህ ሰቀቀኔ ይብሳል ነው?...
[በደንብ ካሰብከው - የሌሎችን ሕማም ለመታመም አይደለም - የራሱን ቁስል ከፍቶ ለማየትም ልቢቱ የሳሳችበት በየቤቱ ብዙ ነው...]
.
.
.
ይልቅ ምን አለ መሰለህ?...
ሰሚህ በችግርህ ውስጥ ጉድለቱን እያየ ከሰማህ - አደመጠህ አይባልም - ተነፈስክበት እንጂ...
ሰሚህ ስለሰማህ ድብርት ከተጫነው - አደመጠህ አይባልም - ጫንክበት እንጂ...
'ይህችማ ምን አላት? እኔ የደረሰብኝን ብታውቅ...' ብሎ ከመለሰልህ - አደመጠህ አይባልም - ቁስልህን ካደብህ እንጂ...
እና እንዳልኩህ ነው...
አንዳንድ ጊዜ... ለብቻህ የምትሸከመው መስቀል ይኖርሃል!!...
____
@bridgethoughts
.
.
.
የዓለማችን 'ግዙፍ ሚዲያዎች' - የቀን ውሎ 90% ያህሉ - በጦርነት፣ በሽብር፣ በግጭትና በጉስቁልና ዜናዎች ብቻ ይሸፈናል ቢባል ድምዳሜው ግነት ተጭኖታል አያስብልም...
በጎ ነገር ባለበት በጭራሽ ዝር አይሉም - ቢሉም እንኳ ደጉን ለመዘገብ ሊሆን አይችልም... ይልቁን በሰርግህ ዕለት ተገኝተው ያንተ ደስታ ለሌሎች የሃዘን ምክንያት ሊሆን የሚችልበትን መንገድ በዘገባቸው በማንሳት ሊያስገርሙህ ይችላሉ...
ይህ በተዘዋዋሪ የሚፈጥረው ጫናና ውጥረት ቀላል አይደለም...
ዓለሚቱ አንዳችም በጎ ነገር የሌላት መስላ ስትቀርብ ዕለታዊ መስተጋብራችን ድንዛዜ ይዋረሰዋል... ተስፋ መቁረጥና ሕይወትን አጨልሞ የማየት አባዜ ይጫነዋል...
ምዕራባውያን ሚዲያዎች ከበጎ ነገር ይልቅ 'ክፉው' ላይ ብቻ የሚረባረቡበት ምክንያት ምንም ይሁን የሚቃኙበት Editorial policy ግን አስገራሚም አሳዛኝም ነው...
ይህን እውነት ይዘን በልካቸው ስናወራ እንዲህ እንላቸዋለን...
CNN - Continuous Negative News
BBC - Brutal Biased Channel
AFP - All Fear Press
NYT - Not Your Truth
____
@bridgethoughts
.
.
.
彡 Title - Three Seconds before Goodbye
彡 Artist - Sia, ft. Damian Marley
___
@bridgethoughts